ለሀገር አቀፉ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት የሚያግዙና የክልሎችን የላብራቶሪ አቅም ለማጐልበት የሚረዱ አንድ ቢሊየን ብር የሚገመቱ የላብራቶሪ መሳሪያዎችና ተሽከርካሪዎች ርክክብ ተከናወነ፡፡

ለሀገር አቀፉ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት የሚያግዙና የአስራ ሶስት ክልሎች የላብራቶሪ አቅም ለማጐልበት የሚረዱ አንድ ቢሊየን ብር የሚገመቱ የላብራቶሪ መሳሪያዎችና ተሽከርካሪዎች ርክክብ ሥነ-ሥርዓት በዛሬው ዕለት በኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ቅጥር ግቢ ውስጥ ተከናወነ፡፡
ዶ/ር መቅደስ ዳባ የጤና ሚኒስትር በርክክብ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር የጤና ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር የክልሎችን አቅም ለማጐልበት ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል አንዱ በሁሉም ክልሎች የክልል የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩቶችን የክልል ላቦራቶሪዎችን መገንባት እና አስፈላጊ የሆኑ ግብዓቶችን በማሟላት ከሁሉም ክልሎች ጋር በቅርበት መስራት መሆኑን ጠቅሰው ከዚህ ቀደም በግሎባል ፈንድ ድጋፍ ከተገነቡ የክልል ላቦራቶሪዎች እና እየተገነቡ ካሉ አስራ ሶስት ላቦራቶሪዎች በተጨማሪ፤ በአሁኑ ወቅት ከዓለም ባንክ አፍሪካ ሲዲሲ ፕሮጀክት በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ከአስራ አራት በላይ አዳዲስ ላቦራቶሪዎች በመገንባት እና አስፈላጊውን መሣሪያዎች ሁሉ በማሟላት ወደ ሥራ በማስገባት ላይ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡
ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ የጤና ሚኒስቴር የማይበገር የጤና ስርዓት ለመፍጠር አቅዶ እየሰራበት መሆኑን አውስተው ለእዚህም በሀገር አቀፍ ደረጃ የላቦራቶሪዎችን አቅም መገንባት ብሎም ከጎረቤት ሀገራት ጋር በቅንጅት መስራት እጅግ አስፈላጊ መሆኑ አብራርተዋል፡፡ ሚኒስትር ዴኤታው አይይዘውም ይህ ድጋፍ የክልሎችን አቅም በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያሳድገው አስረድተው ፕሮጀክቱ ውጤታማ ይሆን ዘንድ አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላት በሙሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
ዶ/ር መሳይ ሀይሉ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከሚተገብራቸው ተግባራት አንዱ በሀገር አቀፍ ደረጃ ላቦራቶሪዎችን አቅም በመገንባት አለም አቀፍ የጥራት ደረጃን የጠበቀ የላብራቶሪ ምርመራ አገልግሎት መሰጠት እንዲችሉ በመደገፍ ለህብረተሰብ ጤና አደጋዎች፣ ቁጥጥርና ፈጣን ምላሽ፣ ለጤና እንክብካቤና ሕክምና አገልግሎት ጥራት መሻሻል እንዲሁም ለጤናና ጤና-ነክ ሳይንሳዊ ምርምሮች ስኬታማነትና ውጤታማነት ተገቢውን አስተዋፅኦ ኢንዲያደርጉ ማስቻል መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ዋና ዳይሬክተሩ አያይዘውም ኢንስቲትዩቱ መጠነ ሰፊ የጤና ላቦራቶሪዎች አቅም ግንባታ ሥራዎችን ከጤና ሚኒስቴርና ክልሎች ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በማከናወን በሁሉም ክልሎች የክልል ጤና ላቦራቶሪዎች አቅም ግንባታ መርሃ-ግብሮችን የሚመሩና የሚተገብሩ የክልል ሪፈረንስ ላቦራቶሪዎች እንዲቋቋሙና እንዲጠናከሩ ማድረግ ከማስቻሉም በላይ የጤና ላቦራቶሪዎች የተሻለ ጥራት ያለው የምርመራ አገልግሎት መስጠት እንዲቻል ዘርፈ ብዙ የአቅም ግንባታ ሥራዎች እያከናወነ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ዶ/ር ሳሮ አብደላ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር በበኩላቸው በሀገር አቀፍ ደረጃ በላብራቶሪዎች ዙርያ እየተከናወኑ ባሉ እና ተያያዥ ስራዎች ዙርያ ለተሰብሳቢዎቹ ገለጻ አድርገዋል፡፡
በዕለቱ ፕሮግራም ላይ እንደተገለጸው የላቦራቶሪ ዘርፉን በበለጠ ማጠናከር ለቅድመ ወረርሽኝ ጥንቃቄና መከላከያ ዝግጅት ሲባል የታወቁ ወረርሽኝ አምጪ ተዋህሲያን ስርጭት ሁኔታን ለመተንተንና ለመረዳት የሚከናወኑ የዳሰሳ ጥናቶች ቅኝቶችና ሌሎች የምርምር ሥራዎች ለመስራት አስፈላጊ ነው፡፡
በተለይም እንደ አዲስ የሚከሰቱትንና ደግመው የሚነሱትን አደገኛ ወረርሽኞችን ትክክለኛ መንስኤዎችን በላቦራቶሪ በመለየት ተገቢው የመከላከልና የቁጥጥር እርምጃዎች እንዲወስዱ በማስቻልና በሁሉም የአገራችን መውጫ እና መግቢያ ኬላዎች አቅራቢያ ደረጃውን የጠበቀ ሪፈራል የላቦራቶሪ ምርመራ አገልግሎት ማደራጀት እጅግ አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበትና የሚያሰፈልገውን ሀብትም በማፈላለግ ከዓለም ባንክ ፕሮጀክት ድጋፍ አስራ አምስት ላቦራቶሪዎች ግንባታ ስራ የተከናወነ ሲሆን እነዚህም ላቦራቶሪዎች በዋናነት ለህብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ሥርዓት ለጤናው እንክብካቤና ህክምና ዘርፍ እንዲሁም ለጤና እና ጤና-ነክ ምርምሮች ተደራሽ በማድረግ ረገድ ትልቅ አቅም የሚጨምሩ እንደሆነ ይገመታል፡፡
በሀገር አቀፍ ደረጃ የጤና ላቦራቶሪ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ ይቻል ዘንድ ቴክኖሎጂ እና ኢንፍራስትራክቸርን ለማስፋፋት እየተሰሩ ካሉ ሥራዎች ጐን ለጐን ጥራት ያለው አገልግሎትን ለመስጠትና ተደራሽነትን ለማስፋት እንዲቻል ከአራት ሺህ በላይ የጤና ተቋማትን ከተለያዩ ላቦራቶሪዎች ጋር ኔት-ወርክ በማድረግ የተሳለጠ የናሙና ቅብብሎሽ እና የውጤት አመላለስ ላይ ከኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት ጋር ውል በመግባት መጠነ-ሰፊ ሥራ እየተሰራ ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅት ሊደርስባቸው ያልቻላቸው ገጠራማ ቀበሌዎችንም በተመለከተ ደግሞ የአማራጭ የናሙና ቅብብሎሽ እና የውጤት አመላለስ ሥርዓት በመዘርጋትና በመተግበር የላቦራቶሪ ምርመራ አገልግሎቶች ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች ሁሉ ተደራሽ እንዲሆን ሌሎች ልዩ ልዩ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን በፕሮግራሙ ላይ የተገለጸ ሲሆን እነዚህ ልዩ ልዩ መሳሪያዎች ከዓለም ባንክ በተገኘ ድጋፍ የተገዙ መሆናቸውንም ለማወቅ ተችሏል፡፡
በመሆኑም አሁን እየተከናወኑ ካሉት ልዩ ልዩ የአቅም ግንባታ እና የመሠረተ ልማት ግንባታዎች በተጨማሪ፤ እነዚህ ለክልሎች ድጋፍ የተደረጉት የላቦራቶሪ መሳሪያዎች ተተክለው ስራ ላይ ሲውሉ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከዚህ በፊት ሲሰጥ የነበረውን የላቦራቶሪ አገልግሎት በበለጠ የሚያሻሽሉ እና በጥራትም፣ በፍጥነትም ህብረተሰቡን የበለጠ የጤና አገልግሎት ተጠቃሚ እንደሚያደርጉ ይታመናል፡፡
በተጨማሪም በኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የተጓዦችና ድንበር ጤና ዳሬክቶሬት ድንበር ተሻጋሪ ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል መጠነ ሰፊ ስራዎችን እየሰራ ሲሆን በመግቢያና መውጫ ኬላዎች ላይ ያለውን የባለሙያዎች የትራንስፖርት እና የናሙዎችን ወደ አቅራቢያ የጤና ድርጅት ወይም ሪጅናል ላቦራቶሪ ለማጓጓዝ ችግር ለመፍታት የ52 ሞተር ሳይክሎች ግዥ በመጠየቅ፣ የግዥ ሂደቱን በመከታተል እንዲገዙ በማድረግ ለሁሉም መግቢያና መውጫ ኬላዎች አራት አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያወች እንደሚከፋፈሉ ተገልጿል።