በሞሪንጋ ላይ ሲደረግ የነበረው የጥናትና ምርምር ፕሮጀክት በመጠናቀቁ የተገኙ ውጤቶችን ለማስተዋወቅ አውደ ጥናት እየተካሄደ ነው

የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በሞሪንጋ እጽዋት ላይ ሲደረግ የነበረው ምርምር ፕሮጀክት በመጠናቀቁ የተገኘውን ውጤትና ግኝት ለማስተዋወቅ ብሎም ለተሳታፊ የትምህርት ተቋማትና
ተመራማሪዎች ምስጋና እና እውቅና ለመስጠት ከየካቲት 18 እስከ 21 2013 ዓ.ም በአርባ ምንጭ ከተማ በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ዓወደ ጥናት በማካሄድ ላይ ነው፡፡ የአውደ ጥናቱ ዋና ዓላማ በሞሪንጋ (አለኮ፣ሺፈራው) እጽዋት ላይ ተክሉ በብዛት በሚበቅለበትና ለጠቀሜታ በሚውልበት አካባቢ ለሶስት አመት ተኩል በተለያዩ የሞያ ዘርፎች ሲካሄዱ የነበሩ ጥናቶች በመጠናቀቃቸው፤የጥናት ውጤቶችንና ግኝቶቹን
በአውደ ጥናቱ በማቅረብ የቀጣይ አቅጣጫዎችን ለመቀየስ፣ በጥናታዊ ውጤቶቹ መረጃ መሰረት ሕብረተሰቡን በማስተማር ተጠቃሚ ለማድረግ እንዲሁም በጥናቱ ተሳታፊና ተባባሪ ለነበሩ ተቋማትና ግለሰቦች የእውቅና ሰርተፍኬት እና ምስጋና
ለማቅረብ የተዘጋጀ ነው፡፡
ዶ/ር ጌታቸው ቶሌራ የኢንስቲትዩቱ ም/ዋና ዳይሬክተር በአውደ ጥናቱ የመክፈቻ ስነ-ስርዓት ወቅት እንደገለጹት የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በምርምር ዘርፍ ከሚሰሩ በርካታ የምርምር አጀንዳዎች መካከል የባህላዊና ዘመናዊ
መድሃኒቶችን በዘመናዊና ሳይንሳዊ ጥናቶች ለመደገፍ የትኩረት አቅጣጫ በማድረግ ከሃገር ውስጥና ከአለም-ቀፍ ባለድርሻ አከላት ጋር የሚያከናውናቸው የጥናትና ምርምር ሥራዎች ጉልህ ሥፍራን እንደሚይዙ፤በተለይ ሓለኮ በሀጋራችን ከቅርብ ጊዜ
ወዲህ ትኩረትን እየሳበ የመጣና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው ሀገር በቀል እጽዋት መሆኑን እና በደቡብና ደቡብ ምዕራብ የሀገራችን ከፍሎች ለሰውና ለእንስሳ የምግብ ምንጭ በመሆን፣ለመድሃኒትነት እና ውሃን ለማጣራት ወዘተ..የሚያገለግል
መሆኑን አብራርተዋል፡፡
በሃለኮ ዙሪያ ያሉትን የዕውቀት ክፍተቶች በመፈተሸና የተበጣጠሱ ሥራዎችን ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው በምግብና በጤና፤ በግብርና እና ደን ምርምር፣በማህበራዊ ኢኮኖሚ ዙሪያ ያለውን ጤቀሜታ በቴክኖሎጂ በመታገዝ ምርቱ ገበያ ላይ
እንዲወል ማድረግ እንደሚገባ ም/ዋና ዳይሬክተሩ አያይዘው ተናግረዋል፡፡
ዶ/ር ዳመጠው ደርዛ የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት የእንኳን ደህና መጣችሁና የመክፈቻ ንግግር ያደረጉ ሲሆን የአርባ ምንጭ ከተማ ከቱሪስት መስህብነቷ አንጻር ለሃገር እያበረከተች ያለችውን ከፍተኛ ጥቅም እንዲሁም የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ አመሰራረትና እድገት በተለይም በሞሪንጋ ላይ ያደረገውን ከፍተኛ የምርምር ስራ አስመልክተው ገለጻ አድርገዋል፡፡ ዶ/ር አስፋው ደበላ የኢንስቲትዩቱ መሪ ተመራማሪ እና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ የጥነቱን ግኝት በጽሁፍ ያቀረቡ ሲሆን ሞሪንጋ
ለምግብነት፣ለመድሃኒትነት ፣ከግብር እና ደን አንጻር እንዲሁም አካባቢን ከማስጠበቅ አኳያ የሚሰጠው ጥቅም የጎላ መሆኑን ጠቅሰው ውጤቱም የበርካታ ተቋማት እና ተመራማሪዎች ቅንጅታዊ ስራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በጥናቱ ወቅት የተገኙ ልምዶችን የማካፍል፣ እውቀቶችን ወደ ተግባር የመለወጥ እና የሃለኮ የምርምር ውጤቶችን ለማሳደግ የሚያስችል የቀጣይ አቅጣጫ ማስቀመጥ እንዲሁም ውጤቱ በምርምር ጥራዝ ተዘጋጅቶ ጥቅም ላይ እንዲውል የማድረግ ስራ
ከአውደ ጥናቱ የሚጠበቁ መሆናቸውን ከአስተባባሪው ለማወቅ ተችሏል፡፡ በጥናቱ ለተሳተፉ 13 የምርምርና ትምህርት ተቋማት የሽልማት ስጦታ እንዲሁም ለ77 ተመራማሪዎች ደግሞ የምስጋና እና
የእውቅና ሰርተፍኬት ተሰጥቷል፡፡ የኢንስቲትዩቱ እና የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፣ የምርምርና ትምህርት ተቋማት ተመራማሪዎች፣ባለድርሻ አካላት፣ጥናት የተካሄደባቸው የወረዳ አመራርና የሕብረተሰብ ተወካዮች በአውደ ጥናቱ ላይ እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡