የህብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ማእከላትን በወረዳዎች ደረጃ ማጠናከር አስፈላጊ ነው ተባለ

በሃገር አቀፍ ደረጃ በሁሉም ክልሎች የሚገኙ ወረዳዎች ላይ የህብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ማዕከላትን የማጠናከር ስራ ተግባራዊ ለማድረግ በኢንስቲትዩቱ በኩል የተገዙትን 300 ሞተር ሳይክሎች ለክልል ጤና ቢሮ እና ለክልል ህብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ሃላፊዎች የኢንስቲትዩቱ ከፍተኛ ሃላፊዎች በተገኙበት ርክክብ ተደርጓል፡፡
የሞተር ሳይክል ለወረዳዎች ድጋፍ ያስፈለገበት ዋና አላማ የህብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ማዕከል በወረዳዎች ደረጃ ለማጠናከር እና ለመኪና አመቺ በልሆኑ ቦታዎች የሚፈጠሩን የመረጃ ክፍተቶችን በመቅረፍ ወቅቱን የጠበቀና በሰዓቱ፣ የእለታት ብሎም የሳምንታት መረጃዎችን እንዲሁም ሪፖርቶችን ለሚመለከተው አካል በተገቢው መንገድ ተደራሽ ለማድረግ ነው፡፡
ዶ/ር ኤባ አባተ የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር በርክክብ ስነ-ስርዓቱ ወቅት አሁን ባለው አለም አቀፍ ሁኔታ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ ያለው የህብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ላይ መሆኑን፣ እንደ ኢንስቲትዩቱም ከክልል እስከ ወረዳ የህብረተሰብ ጤና አደጋዎች መቆጣጠሪያ ማእከላትን ለማጠናከር በርካታ ስራዎች እየተሰሩ ሞሆናቸውንና ለመኪና አመቺ ያለሆኑ ቦታዎችን የተለያዩ መረጃዎችን ተደራሽ ለማድረግ የሚያግዙ 43.5 ሚሊዮን ብር ወጪ ተደርጎ የተገዙትን ሞተር ሳይክሎች ለተፈለገው አላማ በማዋል ውጤታማ ማድረግ እንደሚገባ አብራርተዋል፡፡
የኢንስቲትዩቱ የህብረተሰብ ጤና አደጋ ቁጥጥር ማእከል እስካሁን ያከናወናቸውን ተግባራትና እና ውጤታማ ሆነባቸውን እንዲሁም በቀጣይ ተግባራዊ ሊያደርጋቸው ያቀዳቸውን ስራዎች በዝርዝርና በጽሁፍ በአቶ አብዮት በቀለ የቀረበ ሲሆን ድንገት የሚከሰቱ በሽታዎችን ከመከላከልና ምላሽ ከመስጠት አንጻር የተሰሩ ስራዎችን ደግሞ አቶ መስፍን ወሰን በጽሁፍ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡
የክልል ጤና ቢሮዎች እና ከክልል የጤና አደጋዎች ቁጥጥር ሃላፊዎች የተለያዩ ጥያቄዎችና እስተያየቶች የቀረቡ ሲሆን ከኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተርና ምክትል ዋና ዳይሬክተር በቂ ምላሽ ተሰጥቶበት የሞተር ሳይክል ቁልፍ ርክክብ ተካሂደዋል፡፡
ሞተር ሳይክሎቹን በየክልል ጤና ቢሮዎች የማድረሱን ስራ የሚሰራው ኢንስቲትዩቱ መሆኑንና በየወረዳዎቹ እንዲደርሱ እንዲሁም ለተፈለገው አላማ እንዲውሉ የማድረግ ሃላፊነት የክልሎች፣ የዞኖች እና የወረዳ ጤና አመራሮች መሆናቸውን አቶ እንዳልክ ሲሳይ ገልጸዋል፡፡